ታዋቂው የቴክኖሎጂ ኩባንያ አፕል ከዚህ ቀደም ከነበሩት የላቁ ናቸው የተባሉትን አይፎን 13 ስልኮችንና አዲስ አይፓድ አስተዋወቀ።
በዚህም አፕል አራት ስልኮችን ያስተዋወቀ ሲሆን እነሱም አይፎን 13 ሚኒ፣ አይፎን 13፣ አይፎን 13 ፕሮ እና አይፎን 13 ፕሮ ማክስ የተባሉ ናቸው።
አይፎን 13 ፕሮ እና አይፎን 13 ፕሮ ማክስ ከጀርባቸው ሦስት ካሜራዎች ተገጥመውላቸዋል። አፕል ካሜራዎቹ “እጅጉን የረቀቁ የካሜራ ሥርዓት ናቸው” ብሏል።
አፕል ያስተዋወቃቸው አዲሶቹ አይፎን 13 ስልኮች ይዘው ከመጡት ገጽታዎች [ፊቸሮች] መካከል የበርካቶችን ቀልብ የሳበው፤ ‘በፖርትሬይት ሞድ’ ቪዲዮ መቅረጻቸው ነው።
ከዚህ ቀደም ከአይፎን 7 ወዲህ ያሉ የአፕል ስልኮች በፖርትሬይት ሞድ ፎቶ ማንሳት እንጂ ቪዲዮ መቅረጽ አያስችሉም ነበር።
ፖርትሬይት ሞድ ለምሳሌ አንድን ሰው ከጀርባው ያለውን ዳራ በማደብዘዝ ፎቶ በሚነሳው ሰው ላይ ብቻ ትኩረት በማድረግ ቀልብ መሳብ የሚችል ምስል ማንሳት ያስችላል።
አይፎን 13 ደግሞ ይህን ወደ ቪዲዮ ከፍ አድርጎታል። የአፕል ኩባንያ አለቃ ቲም ኩክ እንደሚሉት ከሆነ ተጠቃሚዎች በፕሮትሬይት ሞድ ቪዲዮ ከቀረጹ በኋላ ኤዲት ማድረግ የሚያስችለው አይፎን-13 ስልክ ብቻ ነው ይላሉ።
ከዚህ በተጨማሪ አዳዲሶቹ አይፎን ስልኮች ተግባራትን በፍጥነት መከወን የሚያስችል ሥርዓት ተዘርግቶላቸዋል።
የስክሪን ግጽታቸው የተሻለ ብርሃን አለው። የባትሪ አገልግሎት ከዚህ ቀደም ከነበሩት አይፎን ስልኮች በ2.5 ሰዓት ከፍ እንዲል ተደርጓል። ከዚህ በተጨማሪም አይፎን 13 ስልኮች በሮዝ፣ በሰማያዊ እና በቀይ ቀለማት አሸብረቀው መጥተዋል።

አዳዲሶቹ አይፎኖች ሚሞሪ መጠንም ወደ 500 ጊጋ ባይት ከፍ ብሏል። በአይፎን-12 ምርቶች ውስጥ ዝቀተኛ ሚሞሪ 64 ጊጋ ባይነት ነበር። አይፎን-13 ግን ዝቅተኛ የመያዝ አቅሙ ወደ 128 ጊጋ ባይት ከፍ እንዲል ሆኗል።
አፕል ብዙ ደክሞ የተለያየ ‘ፊቸር’ ያላቸውን ስልኮች ይፋ ከሚያደርግባቸው ምክንያቶች መካከል ዋነኛው የቀደመውን አይፎን ስልክ የያዙ ደንበኞቹ በአዳዲስ ሞዴሎች እንዲተኳቸው ለማበረታታት እንደሆነ የቴክኖሎጂ ባለሙያዎች ይናገራሉ።
ይሁን እንጂ የኢንቨስትመንት ተቋሙ ዌብቡሽ እንደሚለው በመላው ዓለም የሚገኙ የአፕል ምርት የሆኑ ስልኮችን የያዙ 250 ሚሊዮን ሰዎች ባለፉት 3.5 ዓመታት ስልካቸውን በአዲስ አይፎን ሞዴል አልቀየሩም።

ዋጋ
አይፎን 13 ሚኒ ከ938 ዶላር ጀምሮ፣ አይፎን 13 ከ1076 ዶላር ጀምሮ፣ አይፎን 13 ፕሮ ከ1312 ዶላር ጀምሮ እንዲሁም አይፎን 13 ፕሮ ማክስ 1450 የአሜሪካ ዶላር ጀምሮ ለገበያ ቀርበዋል።
እያንዳንዱ አይፎን 13 ስልክ እንደ ሚሞሪ መጠኑ ዋጋው ይለያያል።

አፕል ዎች 7 እና አይፓድ

አፕል ከስልክ በተጨማሪ ተሻሽሎ የቀረበውን አዲሱን አፕል ዎች አስተዋውቋል።
አዲሱ አፕል ዎች 7 የገዘፈ ስክሪኑ ላይ ኪቦርድ ተግጥሞለታል። አቧራ መቋቋም ይችላልም ተብሏል።
የአፕል ኩባንያ አለቃ ቲም ኩክ አዲሶቹን የአፕል አይፓዶች ሲያስተዋውቁ፤ የአይፓድ ሽያጫቸው ባለፈው ዓመት 40 በመቶ ማደጉን ተናግረዋል።
በኮቪድ-19 ምክንያት ትምህርት ቤቶች ተማሪዎቻቸውን በኢንተርኔት አማካኝነት ለማስተማር መገደዳቸው የአይፓድ ተፈላጊነትን ጨምሮታል።
አዲሶቹ አይፓዶች ከዚህ ቀደም ከነበሩት የአፕል አይፓዶች 20 በመቶ የፈጠኑ ይሆናሉ ብለዋል።

የአፕል አይፓዶች ከ329 የአሜሪካ ዶላር ጀምሮ ለገበያ ቀርበዋል።
በአሁኑ ወቅት በመላው ዓለም በርካታ ስማርት ስልኮችን ለገበያ በማቅረብ የደቡብ ኮሪያው ሳምንስንግ መሪነቱን እንደያዛ ነው። አፕል ደግሞ ሦስተኛ ደረጃን ይዟል።
የቻይና ኩባንያ የሚያመርታቸው ዢዮሚ ስልኮች በገበያ ደርሻ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። ኦፖ እና ቪቮ የተሰኙት ስልኮች ደግሞ አራተኛ እና አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል።